መጣጥፎች



በአላህ ስም እጅግ በጣም ሩህሩህ በጣም አዛኝ በሆነው





እስልምና የዓለማት ጌታ ሃይማኖት





ጌታህ ማን ነው?





ይህ በፍጥረተ ዓለሙ ውስጥ ትልቁ ጥያቄ ነው። ማንኛውም ሰው መልሱን ማወቅ ያለበት በጣም አስፈላጊው ጥያቄም ነው።





ጌታችን ያ ሰማያትንና ምድርን የፈጠረ፤ ከሰማይም ውኃን ያወረደ፤ በርሱም ለእኛና ለእንስሶች ምግብ ይሆነን ዘንድ ፍራፍሬና ዛፎችን ያወጣ (ያበቀለበት) ነው።ጌታችን እኛን የፈጠረን፤ አባቶቻችንንም የፈጠረ፤ ሁሉንም ነገር የፈጠረው እርሱ ነው። ሌሊትንና ቀንን ያደረገም እርሱ ነው፤ ሌሊትን የመኝታና የዕረፍት ጊዜ ቀኑን ደሞ ሲሳይና ቀለብን መፈለጊያ ጊዜ ያደረገ ጌታ ነው።ጌታችን ፀሐይን፣ ጨረቃን፣ ከዋክብትንና ባሕሮችን ያገራልን የምንበላባቸውንና ከወተታቸውም ከፀጉራቸውም የምንጠቀምባቸውን እንስሳትንም ያገራልን ጌታ አሏህ ነው።





የዓለማቱ ጌታ መገለጫ ባህሪዎች ምንድን ናቸው?





ጌታ ፍጥረትን የፈጠረ ነው። ወደ እውነትና ቀናነት የሚመራቸውም እርሱ ነው። የፍጡራንን ጉዳይ ባጠቃላይ የሚያስተናብረው እርሱ ነው። ሲሳይን የሚሰጣቸውም እርሱ ነው። በቅርቢቱም ሆነ በመጨረሻይቱ ዓለም ያለውን ሁሉ ባለቤቱ እርሱ ነው። ሁሉም ነገር የርሱ ንብረት ነው። ከርሱ ውጪ ያለው ሁሉ የርሱ ባርያ ነው።እርሱ የማይሞትና የማይተኛ ሕያው ጌታ ነው። እርሱ ሕያው የሆኑ ፍጥረታት ሁሉ የቆሙት በትእዛዙ የሆነ በራሱ የተብቃቃ (ራሱን ቻይ) ጌታ ነው። እዝነቱ ሁሉንም ነገር የሰፋች፤ እርሱ በምድርም ሆነ በሰማይ ውስጥ ምንም የማይደበቅበት ጌታ ነው።እርሱን የሚመስለው ምንም ነገር የለም፤ ​​እርሱም ሰሚው ተመልካቹ ነው። እርሱም ከሰማያት በላይ የሆነና ከፍጡራኑም የተብቃቃ ነው። ፍጥረታትም ከርሱ ፈላጊዎች ናቸው። እርሱ በፍጥረቱ ውስጥ አይሰርፅም።  ከፍጡሩም በርሱ ዛት ላይ የሚሰርፅ የለም። እርሱ ጥራት የተገባውና ከፍ ያለ ነው።ጌታ እርሱ የሰውንም ይሁን የእንስሳትን አካላትም ሆነ በዙሪያችን ያሉ የአጽናፈ ዓለማት ሥርዓቶችን እንደ ፀሐይ፣ ከዋክብትና ሌሎችም ፍጡራኑን ዝንፍ በማይል ሚዛኑና ሥርዓቱን በጠበቀ መልኩ ይህንን የሚታየውን ዓለም የፈጠረ ነው።





ከርሱ ውጪ የሚመለኩ ሁሉ ለራሳቸው ምንም ጥቅምም ይሁን ጉዳት የማይችሉ ሆነው ሳለ ታዲያ እነርሱን ለሚገዛቸው ጥቅም ማምጣትን ይሁን ጉዳት መከላከልን እንዴት ይችላሉ?





ጌታችን በኛ ላይ ያለው ሐቅ ምንድን ነው?





ጌታ በሰዎች ሁሉ ላይ ያለው ሐቅ እርሱን ብቻ ሊያመልኩ እና በእርሱ ምንንም ላያጋሩ ነው። ከርሱ ውጪም ሆነ ከርሱ ጋር ሰውን ፣ ድንጋይን ፣ ወንዝን ፣ ግዑዝ ነገርን ፣ ኮኮብንም ሆነ ማንኛውንም ነገር ማምለክ አይገባቸውም። ይልቁንም አምልኮን አጥርተው ለዓለማቱ ጌታ ለአላህ ብቻ ነው ማድረግ ያለባቸው።





ሰዎች በጌታቸው ላይ ያላቸው ሐቅ ምንድን ነው?





ሰዎች አላህን በብቸኝነት ካመለኩት አላህ ላይ ያላቸው መብት: በውስጧ ደህንነትን፣ ሰላምን፣ መረጋጋትን፣ ደስታን እና እርካታን የሚያገኙበት መልካም ኑሮን ሊሰጣቸው፤ በመጨረሻው ዓለም ደግሞ ዘውታሪ ችሮታና ዘላለማዊ ፀጋ ባለባት ጀነት ውስጥ ሊያስገባቸው ነው። እርሱን ካመፁና ትእዛዙን ከጣሱ ደግሞ፡ በደስታና በምቾት ውስጥ እንዳሉ ቢያስቡም ሕይወታቸውን አሳዛኝና አስከፊ ያደርግባቸዋል፡። በመጨረሻው አለምም ከሷ የማይወጡባት እሳት ውስጥ ያስገባቸዋል። ለነርሱም በውስጧ ዘላለማዊ ስቃይ አለላቸው።







 







የመኖራችን ዓላማ ምንድን ነው? ለምንስ ፈጠረን?





የተከበረው ጌታችን ለተከበረ አላማ እንደፈጠረን ያም እርሱን ብቻ እንድናመልከው እና በእርሱ ምንንም እንዳናጋራ መሆኑን ነግሮናል። ምድርንም በመልካምና በማስተካከል እንድናሳምር አዞናል። ከጌታውና ከፈጣሪው ውጪ ያመለከ ሰው የተፈጠረበትን አላማ አላወቀም። በፈጣሪው ላይ ያለበትን ግዴታም አልተወጣም። በምድር ላይ የሚያበላሽ ሰውም የተመደበበትን የስራ ኃላፊነት አላወቀም።





እንዴት ነው ጌታችንን የምናመልከው?





ከፍ ያለውና የላቀው ጌታችን እኛን ዝም ብሎ አልፈጠረንምም አልተወንምም፤ ሕይወታችንንም ለጨዋታ አላደረገም። ይልቁንም ከሰዎች መካከል ወደ ህዝባቸው መልዕክተኞችን መረጠ። እነሱም ፍፁም ስነምግባር ያላቸው፤ ነፍሳቸው የፀዳ፤ ልባቸው የጠራ ናቸው። በነርሱ ላይም መልዕክቱን አወረደ። በመልዕክቱም ሰዎች ከፍ ስላለውና ስለላቀው ጌታ ሊያውቁት የሚገባውን ሁሉ፣ ሰዎች የትንሳኤ ቀን እንደሚቀሰቀሱ ገለፀበት። የትንሳኤ ቀን ማለት የሒሳብና የምንዳ ቀን ነው ።መልዕክተኞቹም ወደ ህዝቦቻቸው ጌታቸውን እንዴት እንደሚገዙ፤ የአምልኮን አደራረግና ጊዜውን፤ በአምልኳቸውም በቅርቢቱም ሆነ በመጨረሻይቱ ዓለም የሚያገኙትን ምንዳ አብራሩላቸው። በእነርሱ ላይ ከመብል፣ ከመጠጥ እና ከጋብቻ ጌታቸው የከለከለውን አስጠነቀቋቸው።  ወደ መልካም ስነ ምግባር መሩዋቸው፤ ከፀያፍ ስነ ምግባርም ከለከሏቸው።





ከፍ ያለውና የላቀው ጌታ ዘንድ ተቀባይነት ያለው ሃይማኖት የትኛው ነው?





አላህ ዘንድ ተቀባይነት ያለው ሃይማኖት እስልምና ነው። እስልምና ሁሉም ነቢያት ያስተላለፉት ሀይማኖት ነው። አላህ በትንሳኤ ቀን ከርሱ ውጪ ያለን ሃይማኖት አይቀበልም። ከእስልምና ውጪ ሰዎች የተቀበሉት ሃይማኖት ሁሉ ከንቱ ሃይማኖት ነው። ለባለቤቱም አይጠቅመውም፤ ይልቁንም በዚህም ሆነ በመጨረሻይቱ ዓለም ለእርሱ ጉዳትን ነው የሚያመጣው።





የዚህ ሃይማኖት (የእስልምና) መሰረቶችና ማዕዘናቶች ምን ምንድን ናቸው?





ይህ ሃይማኖት አላህ ለባሮቹ ያገራው ሃይማኖት ነው።  ትልቁ ማዕዘንም በአላህ ጌትነትና አምላክነት፣ በመላእክቱም፣ በመፃሕፍቱም፣ በመልክተኞቹም፣ በመጨረሻው ቀንና በውሳኔውም ማመን ፤ ከአላህ በቀር በእውነት የሚመለክ አምላክ እንደሌለና ሙሐመድም የአላህ መልእክተኛ መሆናቸውን መመስከር፤  ሶላትንም መስገድ፤ ዘካ ግዴታ የሚሆንበት የገንዘብ መጠን አንተ ዘንድ ካለ ዘካ መስጠት፤ በአመት ውስጥ አንድ ወር የረመዳንን ወር መፆም፤ አቅሙ ካለም ኢብራሂም (ዐለይሂ ሰላም) ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና በጌታቸው ትእዛዝ ወደገነቡት ጥንታዊው ቤት ተጉዞ ለአላህ ብለህ ሐጅ ማድረግ ነው።ሽርክን፣ ነፍስ መግደልን፣ ዝሙትን፣ የተከለከለን ገንዘብ መብላትን እና የመሳሰሉትን አላህ የከለከላቸውን ነገሮች መራቅ አለብህ። በአላህ አምነህ እነዚህን አምልኮዎች ከሰራህና እነዚህን የተከለከሉ ነገሮች ከራቅክ በዚህ አለም ላይ አንተ ሙስሊም ነህ። በትንሣኤ ቀንም አላህ በጀነት ውስጥ ዘላለማዊ ደስታን እና ዘውታሪነትን ይሰጥሀል።





እስልምና ለአንድ ህዝብ ወይም ዘር የመጣ ሀይማኖት ነውን?





እስልምና ለሰዎች ሁሉ የመጣ የአላህ ሃይማኖት ነው። አላህን በመፍራት እና በመልካም ስራ ካልሆነ በስተቀር ማንም ከማንም በላጭነት የለውም። ሰዎችም በእስልምና እኩል ናቸው።





ሰዎች የመልእክተኞቹን (የአላህ ሶላትና ሰላም በነርሱ ላይ ይስፈንና) እውነተኝነት እንዴት ያውቃሉ?





ሰዎች የመልእክተኞችን እውነተኝነት በብዙ መንገድ ያውቃሉ። ከነርሱም መካከል:-





መልክተኞች ይዘውት የሚመጡት እውነትና መመሪያ ንፁህ አእምሮና ጤነኛ ተፈጥሮ ይቀበለዋል፤ አእምሮዎችም ለመልካምነቱ ይመሰክራሉ፤ ከመልክተኞች ውጪም እነርሱ ያመጡትን ብጤ ማንም አያመጣም።





መልእክተኞች ይዘውት የመጡት ነገር የሰዎችን ሃይማኖት እና ዓለማዊ ህይወታቸውን የሚያሻሻል ፤ ጉዳዮቻቸውን የሚያስተካክል ፤ ሥልጣኔያቸውን የሚገነባ እና ሃይማኖታቸውንም፣ አእምሯቸውንም፣ ሀብታቸውን እና ክብራቸውን የሚጠብቅ ነው።





መልእክተኞች (የአላህ ሰላም እሁሉም ላይ ይስፈንባቸውና) ሰዎችን ወደ መልካም እና ቅናቻ በመምራታቸው ክፍያን አይጠይቁም። ይልቁንም ከጌታቸው ዘንድ ነው ምንዳቸውን የሚጠባበቁት።





መልእክተኞች ይዘውት የመጡት ነገር ጥርጣሬ የማይቀላቀለው  እውነት እና እርግጠኛ ነው፤ የማይጋጭና የማይምታታ ነው፤ ሁሉም ነቢይ ሲመጣ ያለፉትን ነቢያት እውነተኝነት ያረጋግጣልም ያለፉት ነቢያት ወደጠሩትም አምሳያ ነው የሚጣራው።





አላህ መልእክተኞችን (የአላህ ሰላም በነርሱ ላይ ይስፈንና) ከአላህ ዘንድ የተላኩ ለመሆናቸው የእውነት ምስክር ይሆን ዘንድ በግልፅ ተዓምራቶች እና አላህ በእጃቸው በሚያደርግላቸው ሀያል ተአምራት ይረዳቸዋል። ለነብያት ከተሰጣቸው ተአምራት ሁሉ ትልቁ ተአምር ለመጨረሻው መልክተኛ ሙሐመድ  (የአላህ ሶላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈንና) የተሰጣቸው ተአምር ነው። እርሱም የተከበረው ቁርኣን ነው።







 





የተከበረው ቁርኣን ምንድን ነው?





የተከበረው ቁርኣን የዓለማቱ ጌታ መጽሐፍ ነው። እርሱም በመልዐኩ ጅብሪል (ዐለይሂ ሰላም) አማካኝነት ወደ መልእክተኛው ሙሐመድ (የአላህ ሶላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈንና) የወረደ የአላህ ቃል ነው። በውስጡም ስለ አላህ፣ ስለ መላእክቱ፣ ስለ መጻሕፍቱ፣ ስለ መልእክተኞቹ፣ ስለ መጨረሻው ቀን እና አላህ ስቀደረው መልካምና መጥፎ እንዲሁም ስለ ሌሎችም አላህ ሰዎችን እንዲያውቁት ያስገደዳቸውን ነገሮች ሁሉ ይዟል።በውስጡም ግዴታ የሆኑ አምልኮዎችን፣ አንድ ሰው ሊጠነቀቃቸው የሚገቡ የተከለከሉ ነገሮችን፣ መልካም እና መጥፎ የሆኑ ሥነ ምግባሮችን፣ እንዲሁም ከሰዎች ሃይማኖት፣ ዓለማዊ ጉዳዮች ጋርና ከሞት በኋላ ሕይወትን የሚመለከቱ ጉዳዮችን ሁሉ አካቶ ይዟል። አላህ ሰዎችን ብጤውን እንዲያመጡ የተገዳደረበት ተአምረኛ መጽሐፍ ነው። እርሱም አንዲትም ቃል ሳይጎድልበትና ሳይለወጥበት በወረደበት ቋንቋ እስከ ትንሣኤ ቀን ድረስ ተጠብቆ የሚኖር ነው።





መቀስቀስና በስራ መተሳሰብ እንዳለ ማስረጃው ምንድን ነው?





ምድር የሞተችና በውስጧ ሕይወት የሌላት ሆና አታይምን፤ ውኃ በወረደባት ጊዜ ግን ትንቀጠቀጣለች ያማረውን ተክልም ሁሉ ታበቅላለች። መሬትን ሕያው ያደረገ ጌታ ሙታንንም ሕያው ማድረግ ይችላል።ሰውን ከደካማ የውሃ ጠብታ የፈጠረ ጌታ በትንሳኤ ቀን ሊያስነሳው፣ ሊተሳሰበውና ሥራው መልካም ከሆነ በመልካም መጥፎም ከሆነ በመጥፎ የተሟላ ምንዳውን ሊመነዳው ይችላል።ሰማያትን፣ ምድርን፣ ከዋክብትን የፈጠረ ሰውን በድጋሚ መፍጠር ላይም ይችላል። ምክንያቱም ሰውን እንደገና መልሶ መፍጠር ሰማያትንና ምድርን ከመፍጠር አኳያ እጅግ የቀለለ ነገር ነውና።





የትንሳኤ ቀን የሚሆነው ምንድን ነው?





የበላይና የላቀው ጌታ ፍጥረታትን ከመቃብራቸው ያስነሳል፤ ከዚያም በሠሩት ሥራ ይተሳሰባቸዋል፤ ያመነና መልዕክተኞችንም እውነት ያለ ሰው ጀነት ውስጥ ያስገባዋል፤ ይህም ታላቅነቱ በሰው ልጅ አዕምሮ ውል ብሎ የማያውቀው ዘላለማዊ ፀጋ ነው። የካደም ሰው እሳት ያስገባዋል፤ ይህም ሰው ሊያስበው የማይችለው ዘላለማዊ ስቃይ ነው። እናም አንድ ሰው ጀነት ወይም ጀሀነም ከገባ ፈጽሞ አይሞትም፤ በፀጋ  ውስጥ ወይም በቅጣት ውስጥ ዘላለማዊና ዘውታሪ ይሆናል።





አንድ ሰው እስልምናን መቀበል ከፈለገ ምን ማድረግ አለበት? እሱ ሊፈፅም የሚገባቸው ሃይማኖታዊ ስርአቶች ወይንም ፍቃድ መስጠት ያለባቸው ሰዎች አሉን?





አንድ ሰው እውነተኛው ሃይማኖት እስልምና መሆኑን እና የዓለማት ጌታ የመረጠው ሃይማኖት መሆኑን ካወቀ ወደ እስልምና ለመግባት መቸኮል አለበት። ምክንያቱም ብልህ ሰው እውነቱ የተገለፀለት ጊዜ ወደ እሱ ይጣደፋል እንጂ ጉዳዩን ለሌላ ጊዜ አያዘገየውምና።እስልምናን መቀበል የሚፈልግ ሰው (እስልምናን ለመቀበል) የተለየ ሃይማኖታዊ ስነስርአት የማድረግ ግዴታ የለበትም። ከሰዎችም ውስጥ በማንም ፊት መሆን  አይጠበቅበትም። ነገር ግን ይህ በሙስሊም ፊት ወይም በኢስላማዊ ማእከል ውስጥ ከሆነ በጎ ላይ በጎን ነው የጨመረው። ያለበለዚያ፡- ትርጉሙን አውቆና  በቃሉ አምኖበት (አሽሀዱ አን ላ ኢላሃ ኢለላህ ወአሽሀዱ አንነ ሙሐመደን ረሱሉላህ) (ትርጉሙም: ከአላህ በስተቀር በእውነት የሚመለክ አምላክ እንደሌለ እመሰክራለሁ፤ ሙሐመድም የአላህ መልእክተኛ መሆናቸውን እመሰክራለሁ።) ካለ በዚህ ሙስሊም ይሆናል። ከዚያም አላህ ግዴታ ያደረገበትን ነገሮች ለመተግበር የተቀሩትን የእስልምና ህግጋቶች ቀስ በቀስ መማር ነው።





 



የቅርብ ጊዜ ልጥፎች

እስልምና የዓለማት ጌታ ሃይማኖት ...

እስልምና የዓለማት ጌታ ሃይማኖት

መልእክት ከሙስሊም ሰባኪ ለክርስቲ ...

መልእክት ከሙስሊም ሰባኪ ለክርስቲያን ሰው

የሸዋል ስድስት ቀናት መፆም በጎነ ...

የሸዋል ስድስት ቀናት መፆም በጎነት SHAWAL

የተከበረው ቁርኣን ምንድን ነው? ...

የተከበረው ቁርኣን ምንድን ነው?